Connect with us

Uncategorized

የዮሐንስ ዋልያዎች በሽንፈት ጀምረዋል

Published

on

Ethiopia vs Zambia - 06072015-2

Ethiopia vs Zambia - 06072015-2

በአሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ የሚመራው አዲሱ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለ2017ቱ የአፍሪካ ዋንጫ እና ለ2016ቱ የቻን ውድድር ላይ ለመገኘት ለሚያደርጋቸው የማጣሪያ ጨዋታዎች ዝግጅቱን ከጀመረ ቀናት ተቆጥረዋል፡፡ በዋልያዎቹ አለቅነታቸው ስኬታማ መሆን ያልቻሉትን ማሪያኖ ባሬቶን ተክተው የአሰልጣኝነት ኃላፊነቱን የያዙት ዮሐንስ ሳህሌ ከኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ 44 ተጨዋቾችን መርጠው ከሁለት ቀናት የልምምድ ጨዋታዎች በኋላ ስብስባቸውን ወደ 24 የቀነሱ ሲሆን፣ ከነዚህ ተጨዋቾች ጋር ካደረጉት የጥቂት ቀናት ልምምድ በኋላ ደግሞ ከዛምቢያ ብሔራዊ ቡድን ጋር የአቋም መለኪያ የወዳጅነት ጨዋታ አድርገዋል፡፡ በበርካታ ወጣት እና የኢንተርናሽናል ጨዋታዎች ልምድ የሌላቸው ተጨዋቾች የተዋቀረው ቡድን እሁድ ከቀትር በኋላ የዛምቢያ አቻውን በሜዳው ለመግጠም ወደ ሜዳ ሲገባ ይዞት የገባው አሰላለፍ የሚከተለው ነበር፡-

ግብ ጠባቂ፡- አቤል ማሞ (ሙገር ሲሚንቶ)

ተከላካዮች፡- ሞገስ ታደሰ (ሲዳማ ቡና)፣ አስቻለው ታመነ (ደደቢት)፣ ሙጂብ ቃሲም (ሀዋሳ ከነማ)፣ ዘካሪያስ ቱጂ (ቅዱስ ጊዮርጊስ)

አማካዮች፡- ጋቶች ፓኖም (ኢትዮጵያ ቡና)፣ ምንተስኖት አዳነ (ቅዱስ ጊዮርጊስ)፣ በኃይሉ አሰፋ (ቅዱስ ጊዮርጊስ)፣ አስቻለው ግርማ (ኢትዮጵያ ቡና)

አጥቂዎች፡- ባዬ ገዛኸኝ (ወላይታ ድቻ) እና ቢኒያም አሰፋ (ኢትዮጵያ ቡና)

በተመሳሳይ በአዳዲስ ወጣት ተጨዋቾች የተገነባው የዛምቢያ ብሔራዊ ቡድንም የሚከተሉትን ተጨዋቾች በመጀመሪያ ተሰላፊነት ተጠቅሟል፡፡

ግብ ጠባቂ፡- ዳኒ ሙኒያኦ (ሬድ አሮውስ / ዛምቢያ)

ተከላካዮች፡- ካባሶ ቾንጎ (ቲ.ፒ ማዜምቤ / ሪ.ዲ.ኮንጎ)፣ አሮን ካቴምቤ (ፕላቲነም / ዚምባቡዌ)፣ ክርስቶፈር ሙንትሀሊ (ፓወር ዳይናሞስ / ዛምቢያ)፣ ፋክሰን ካፑምቡ (ዛናኮ / ዛምቢያ)

አማካዮች፡- ናታን ሲንካላ (ቲ.ፒ ማዜምቤ / ሪ.ዲ.ኮንጎ)፣ ኮንድዋኒ ምቶንጎ (ዜስኮ ዩናይትድ / ዛምቢያ)፣ ሉባምቦ ሙሶንዳ (ኡሊሴስ ዬሬቫን / አርሜኒያ)፣ አለን ሙኩካ (ግሪን ቡፋሎስ / ዛምቢያ)

አጥቂዎች፡- ኤቫንስ ካንግዋ (ሀፖኤል ራአናና / እስራኤል) እና ጊቭን ሲንጉሉማ (ቲ.ፒ ማዜምቤ / ሪ.ዲ.ኮንጎ)

ዝርግ 4-4-2 የመሰለ ፎርሜሽን ይዞ ወደ ሜዳ የገባው በበኃይሉ አሰፋ አምበልነት የተመራው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ጨዋታውን ሞቅ ባለ ስሜት እና እንቅስቃሴ ቢጀምርም መልካሙ እንቅስቃሴው ከ15 ደቂቃዎች ያለፈ አልነበረም፡፡ ቡድኑ ቀስ በቀስ እየወረደ ከ20 እና 25 ደቂቃዎች በኋላ የጨዋታው የበላይነት በዛምቢያዊያኑ እጅ ገብቷል፡፡ በመጀመሪያው አጋማሽ ከባዬ ገዛኸኝ እና ምንተስኖት አዳነ ከሩቅ ተመትተው ኢላማቸውን ካልጠበቁ ሙከራዎች እና ከመስመር ተሻግረው ለጥቂት ለአጥቂዎች ሳይደርሱ ከቀሩ ኳሶች በቀር ዋልያዎቹ የተጋጣሚያቸውን ተከላካዮች ጥሰው ለመግባት እና የጎል ሙከራዎች ለማድረግ የተሳናቸው ሲሆን ተመሳሳይ 4-4-2 ፎርሜሽንን በተሻለ የተጠቀሙበት የመሰሉት ዛምቢያዊያኑ በአንጻሩ በአሮን ካቴምቤ በጭንቅላት ተገጭቶ በግብ ጠባቂው አቤል ድንቅ ጥረት ጎል ከመሆን የተረፈው፣ ሉባምቦ ሙሶንዳ መትቶት ለጥቂት የወጣበት እና ናታን ሲንካላ ከቅርብ ርቀት ሞክሮት በሙጂብ ቃሲም አስደናቂ ሸርተቴ የተመለሰበት የሚጠቀሱ ጥሩ የጎል አጋጣሚዎች መፍጠር ችለዋል፡፡ ቺፖሎፖሎ (ጥይቶቹ) ይህ ጫናቸው በሙከራዎች ብቻ ሳይገደብም በመጀመሪያው አጋማሽ የመጨረሻው ደቂቃ ከአስደናቂ የመልሶ ማጥቃት የተገኘውን እና ከግራ መስመር የተሻገረውን ኳስ በአለን ሙኩካ አማካይነት አስቆጥረው መሪነቱን ይዘዋል፡፡ የዋልያዎቹ የመጀመሪያ አጋማሽ በአጠቃላይ ሲታይ የአማካይ ክፍሉ እና አጥቂ ክፍሉ ግንኙነት መሰበር፣ የሁለቱ የመስመር ተከላካዮች ወደ ፊት ሄዶ ማጥቃቱን ማገዝ አለመቻል እና የሁለቱ አጥቂዎች የቅንጅት ችግር የታየበት ነበር፡፡ ከተከላካይ ክፍሉ የተሻለ ብቃት ሌላም ከዮሐንስ ቡድን የሚጠቀስ መልካም ነገር አልነበረም፡፡

Ethiopia vs Zambia - 06072015-1

ሁለተኛው አጋማሽ የተጀመረው በዋልያዎቹ በኩል ግብ ጠባቂው አቤል በደደቢቱ ታሪክ ጌትነት፣ ጥንዶቹ አማካዮች ጋቶች ፓኖም እና ምንተስኖት አዳነ በወላይታ ድቻው ብሩክ ቃልቦሬ እና በመከላከያው ፍሬው ሰሎሞን ተተክተው ነበር፡፡ ጥይቶቹ ካረፉበት በመቀጠል ይህም አጋማሽ እንደተጀመረ ሁለት ተከታታይ አስደንጋጭ የጭንቅላት የተገጩ ሙከራዎችን ማድረግ ችለዋል፡፡ ነገር ግን የዮሐንስ ልጆች ቀስ በቀስ ጨዋታውን በመቆጣጠር ከመጀመሪያው አጋማሽ በተሻለ መንቀሳቀስም ሆነ እውነተኛ የጎል እድሎችን መፍጠር ችለው ነበር፡፡ ተቀይረው የገቡት አማካዮች ጨዋታውን በበጎ መለወጥ ሲችሉ በተለይም ፍሬው ሰሎሞን ቡድኑ አጥቶት የነበረውን ኳስ ቁጥጥር እና ፈጠራ ማበርከት ችሏል፡፡ የመከላከያው አማካይ ከቢኒያም አሰፋ ጋር አንድ ሁለት ተቀባብሎ በቀጥታ ወደ ጎል ሞክሮት በግብ ጠባቂው ዳኒ ሙኒያኦ ተጨርፎ የወጣበት ሙከራ እጅግ አስደናቂ እና ደጋፊውን በስሜት ያቆመ ነበር፡፡ ከደቂቃዎች በኋላም ራሱ ፍሬው በረዥሙ ለቢኒያም አቀብሎት የኢትዮጵያ ቡናው አጥቂ ለክለብ ጓደኛው አስቻለው ግርማ ያቀበለው እና አስቻለው ወደ ፍፁም ቅጣት ምት ክልል እየገፋ የገባውን ኳስ ሳይጠቀምበት በፊት በዛምቢያው ተከላካይ በመጠለፉ ዋልያዎቹ የፍፁም ቅጣት ምት ማግኘት ችለው ነበር፡፡ ነገር ግን ቢኒያም ወደ አየር በማንሳፍ ሳይጠቀምበት ቀርቷል፡፡ እንደ ሳውዝሀምፕተኑ ኤማኑኤል ማዩካ አይነት ተጨዋቾችን ቀይረው ያስገቡት ጥይቶቹ በተሻሻለው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን እና ምናልባትም በታወቀው የአልቲቲዩድ ተፅዕኖ ምክንያት ሳይሆን አይቀርም በዚህ ግማሽ ከመጀመሪያው አንጻር ተዳክመው ቢታዩም ከላይ ከተጠቀሱት የጭንቅላት ሙከራዎች በተጨማሪ ከታሪክ ጋር ፊት ለፊት ተገናኝተው በግብ ጠባቂው የተመለሰባቸው አይነት ሙከራዎችን ግን አድርገዋል፡፡ ጨዋታው ወደ መጠናቀቂያው ሲቀርብ አምበሉ በኃይሉ አሰፋ እና አጥቂው ባዬ ወጥተው በኤሌክትሪኩ ራምኬል ሎክ እና በሙገር ሲሚንቶው ኤፍሬም ቀሬ ሲተኩ የመሀል ተከላካዩ ሙጂብ በሁለት የማስጠንቀቂያ ካርዶች ከሜዳ ተሰናብቷል፤ ጨዋታውም የዛምቢያ የ1ለ0 ድል ተጠናቋል፡፡

አሰልጣኞቹ ምን አሉ?

አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ፡

“ዓላማችን ከህዝብ፣ ሚዲያ እና ተጋጣሚ ጫና ጋር የመጫወትን ከባድ ኃላፊነት ለወጣቶቹ ተጨዋቾቻችን ለማሳየት ነበር እናም ተሳክቶልናል፡፡እንደ እነ አቤል፣ አስቻለው፣ ዘካሪያስ እና ሙጂብ አይነቶቹ ከጠበቅነው በላይ ጥሩ ሲጫወቱ እነባዬ ትንሽ ተቸግረው ነበር፡፡ ልምድ ካላቸው ከእነበኃይሉም የጠበቅነውን አላገኘንም፡፡”

“በመጀመሪያው አጋማሽ ጋቶች እና ምንተስኖት ያዘዝናቸውን ባለማድረጋቸው አማካይ ክፍሉ ልክ አልነበረም፡፡ ጋቶች የበለጠ በመከላከሉ እና ምንተስኖት የበለጠ በማጥቃቱ እንዲሳተፉ ነግረናቸው ነበር፡፡ ግን ሁለቱም ጎል ለማግባት በመጓጓት ቦታቸውን ጠብቀው መጫወት አልቻሉም፡፡ በሁለተኛው አጋማሽ የቀየርናቸው ብሩክ እና ፍሬው ይህን ችግር ፈትተዋል፤ ቡድኑም ጥሩ መሆን ችሏል፡፡”

“ዓላማዬ የተሰጠኝን ኃላፊነት ለመወጣት የሚያስችለኝን ቡድን መገንባት እንጂ የቀጣዩን ትውልድ ቡድን መገንባት አይደለም፡፡ መቼ ከኃላፊነት እንደምነሳም አላውቅም፡፡”

አሰልጣኝ ኦነር ጃንዛ፡

“ከወሳኝ የማጣሪያ ጨዋታ በፊት እንዲህ አይነት ጠንካራ ጨዋታ በማግኘታችን ኢትዮጵያን እናመሰግናለን፡፡ ቡድናችን በአዲስ መልክ እየተገነባ በመሆኑ ስለሚመጣው ውጤት ፍርሀት አልነበረንም፡፡ ምክንያቱም ጥሩ ቡድን በአንድ ቀን መገንባት አይቻልም፡፡”

“የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ጥሩ ጎኖች አሉት፡፡ ግን ወደፊት ሲሄድ ያለበትን የአጨራረስ እና የቴክኒክ ችግሮች መፍታት ይኖርበታል፡፡”

Ethiopia vs Zambia - 06072015-3

ዋልያዎቹ ሲመዘኑ፡

አቤል ማሞ፡ የሙገር ሲሚንቶው ግብ ጠባቂ በአየር ላይ የሚላኩ ኳሶች ላይ ጥሩ ብቃት ቢያሳይም በተቆጠረው ጎል ላይ ካደረገው የተሻለ ማድረግ ይጠበቅበት ነበር፡፡

ታሪክ ጌትነት፡ ተቀይሮ የገባው ታሪክ ከዛምቢያ አጥቂ ጋር አንድ ለአንድ ተገናኝቶ መመለስ ቢችልም የኳስ ስርጭቱ ደካማ ነበር፤ ይህ ድክመቱ በተወሰኑ አጋጣሚዎችም ችግር ውስጥ ከቶት ነበር፡፡

ሞገስ ታደሰ፡ አግሬሲቩ የሲዳማ ቡና ተከላካይ ከመስመር ተከላካይ የሚፈለገው ቅልጥፍና እና ፍጥነት ሲጎድለው የሚወርዳቸው ሸርተቴዎች አደገኛ ነበሩ፤ ግልፍተኛም ነበር፡፡

አስቻለው ታመነ፡ ይህ ወጣት በአስደናቂ ፍጥነት አስተማማኝ ተከላካይ እየሆነ ነው፡፡ ከጥፋቶች የራቀው ርጉው የደደቢት ፍሬ በመጀመሪያ ኢንተርናሽናል ጨዋታው ጥሩ ጊዜን አሳልፏል፡፡

ሙጂብ ቃሲም፡ የሀዋሳው ተከላካይ በሁለት የቢጫ ካርዶች ከሜዳ ቢወጣም ከአስቻለው ጋር ጥሩ የመሀል ተከላካይ ጥምረት ፈጥሮ ታይቷል፡፡

ዘካሪያስ ቱጂ፡ የዘንድሮው የቅዱስ ጊዮርጊስ ክስተት በመከላከሉ ረገድ ሁሉንም ያስደነቀ ምርጥ እንቅስቃሴ ቢያሳይም ባልተለመደ መልኩ ወደፊት ሄዶ የመስመር አጋሩን በማገዝ ረገድ ጥሩ አልነበረም፡፡ ኳሶች ከቀማ በኋላ በትክክል የማቀበል ስኬቱም መልካም አልነበረም፡፡

ጋቶች ፓኖም፡ ዘንድሮ በሊጉ በኢትዮጰያ ቡና ማልያ በእጅጉ ተሻሽሎ የታየው አማካይ የተሰጠውን ተከላካዮቹን ከጥቃት የመከላከልም ሆነ የቡድኑ ሚዛን የመጠበቅ ኃላፊነቶች መወጣት አልቻለም፡፡

ምንተስኖት አዳነ፡ የቅዱስ ጊዮርጊሱም አማካይ እንዲሁ ሊያስታውሰው የማይወደውን ጨዋታ አሳልፏል፡፡ ምንተስኖት አማካይ እና አጥቂ ክፍሉን የማገናኘት ተግባሩን ሊወጣ አልቻለም፡፡

ብሩክ ቃልቦሬ፡ ጋቶችን ተክቶ የገባው የወላይታ ድቻው አማካይ ለተከላካይ ሽፋን በመስጠት እና የቡድኑን ሚዛን በመጠበቅ ረገድ ተሽሎ ታይቷል፡፡ የኳስ ስርጭቱ ፍጥነት ግን ጥያቄ የሚነሳበት ነበር፡፡

ፍሬው ሰሎሞን፡ ከእረፍት በኋላ ዋልያዎቹ የተሻለ ለመጫወታቸው የመከላከያው አማካይ ወደ ሜዳ መግባት ቀዳሚ ተጠቃሽ ምክንያት ነበር፡፡ የፍሬው ድሪብሎች፣ የሚያቀብላቸው ኳሶች እና ከአጥቂዎቹ ጋር የፈጠረው ቅንጅት በፈዘዘው ቡድን ላይ ነፍስ ዘርተውበታል፡፡

በኃይሉ አሰፋ፡ የፕሪምየር ሊጉ ኮከብ ዝም ያለ ቀትር አሳልፏል፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊሱ አማካይ እንደአምበልነቱ በንግግር ቡድኑን ለመምራት ከመሞከሩ ባለፈ እንቅስቃሴው ጓደኞቹን ለመምራትም ሆነ ለማነሳሳት በቂ አልነበረም፡፡

አስቻለው ግርማ፡ ለእሱ ተፈጥሯዊ ባልሆነ የግራ አማካይ ስፍራ የተጫወተው የኢትዮጵያ ቡናው የመስመር አማካይ/አጥቂ ለፍፁም ቅጣት ምቱ መገኘት ምክንያት ቢሆንም እና የሁልጊዜ ታታሪነቱ ባይለየውም በፈጠራ እና የማጥቃት ስጋት በመፍጠር ረገድ ብዙም ጥሩ አልነበረም፡፡

ባዬ ገዛኸኝ፡ የወላይታ ድቻው አጥቂ ከአጋሩ ጋር መግባባት ሳይችል፣ የሚያገኛቸውንም ኳሶች በሚገባ ለመጠቀምም ሆነ ለማቀበል ተቸግሮ ነበር፡፡

ቢኒያም አሰፋ፡ በተጠናቀቀው የሊግ ውድድር ባለብዙ ጎል ኢትዮጵያዊ የነበረው ቢኒያም ላመከነው የፍፁም ቅጣት ምት እና ለፍሬው አስደናቂ ሙከራ ምክንያት ቢሆንም በአጠቃላይ ግን እምብዛም ጥሩ ያልነበረ ጨዋታን አሳልፏል፡፡

ራምኬል ሎክ እና ኤፍሬም ቀሬ፡ ለምዘና የሚያበቃ የጨዋታ ጊዜ አልነበራቸውም፡፡

አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ፡ ኃላፊነቱን ከያዙ ገና ጥቂት ሳምንታት እንደመቆጠራቸው እና ተጨዋቾቻቸውን ካገኙ ሳምንት እንኳን እንደአለመሙላቱ ለቡድኑ የቅንጅትም ሆነ ሌሎች ችግሮች ትችት ማቅረብ ፍትሀዊ አይሆንም፡፡

ሌሎች ጉዳዮች፡

  • ሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች ጨዋታቸውን ለማድረግ ወደ ሜዳ ሲወጡ ብሔራዊ መዝሙሮቻቸውን በተለመደው መንገድ ከሲዲ ማጫወቻ ወይም ቴፕ ሬከርደር ማሰማት ሳይቻል ቀርቶ ከኳስ አቀባይ ታዳጊ እና ከአንድ የዛምቢያ ቡድን አባል በድምፅ ማጉያ እንዲዘመር መደረጉ እጅግ አነጋጋሪ እና አሳፋሪም ክስተት ነበር፡፡
  • የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከሌሶቶ ጋር የሚያደርገውን ወሳኝ የአፍሪካ ጨዋታ በቀጣዩ እሁድ፣ ሰኔ ሰባት፣ በባህር ዳር ስታዲየም ያካሂዳል፡፡ እዚያው ዝግጅቱን ለማድረግም ወደ ባህር ዳር አምርቷል፤ የሌሶቶ አቻው ሀሙስ ኢትዮጰያ እንደሚገባ ይጠበቃል፡፡
  • በውጪ ሀገራት ከሚጫወቱ እና ለብሔራዊ ቡድኑ ከተጠሩት አራት ተጨዋቾች መካከል የቢድ ቬትሱ ጌታነህ ከበደ እና የፔትሮ ጄቱ ሽመልስ በቀለ እንዲሁም የአሌክዛንድሪያው ኡመድ ኡኩሪ ከቡድኑ ጋር ወደባሕር ዳር ያቀኑ ሲሆን የአል-አህሊው ሳልሀዲን ሰዒድ በቀጣዮቹ ቀናት ቡድኑን እንደሚቀላቀል ይጠበቃል፡፡

 

 

Articles

24ኛው የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና በፖላንድ ግድኒያ ይካሄዳል

Published

on

Gdynia 2020

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ከምስራቅ አፍሪካ አቻዎቻቸው ጋር ለአሸናፊነት ይፎካከራሉ

በባልቲክ ባሕር ዳርቻ የምትገኘው ትንሿ የፖላንድ ወደብ ከተማ ግድኒያ በሀገራት መካከል የሚካሄድ የዓመቱ ብቸኛ ዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ውድድር የሆነውን እና ከሰዓታት በኋላ የሚጀመረውን የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና ለማስተናገድ ዝግጅቷን አጠናቃለች፡፡ ስመ ጥር አትሌቶች የተካተቱበትና ከ250 በላይ ተሳታፊዎች የሚፎካከሩበት ይህ ሻምፒዮና የዓለም አትሌቲክስ ስፖርት አፍቃሪያን አይኖች ዳግም በምስራቅ አፍሪካውያኑ ኮከቦች ላይ እንዲያተኩሩ እንደሚያስገድድ ይጠበቃል፡፡ በሴቶቹ ውድድር ሴቶች ብቻ የተሳተፉበት ሩጫ የዓለም ሪኮርድ ባለቤቷ ኬንያዊት ፐሬስ ጄፕቺርቺር እና በወንዶች አሯሯጭነት የተመዘገበ የዓለም ሪኮርድ ባለቤት የሆነችው ኢትዮጵያዊቷ አባበል የሻነህ፤ በወንዶች በቅርቡ የ5000 ሜትር እና 10000 ሜትር የዓለም ሪከርዶችን የሰባበረው ኡጋንዳዊው ጆሹዋ ቼፕቴጊ እንዲሁም ኢትዮጵያዊው ጉዬ አዶላ ከሌሎች ተፎካካሪዎቻቸው በመላቅ በፖላንዷ የባህር ዳርቻ ከተማ ላይ የወርቃማ ድል አሻራቸውን ለማሳረፍ ተስፋ ከሚያደርጉት ከዋክብት መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

Photo Aman @angasurunning

ከ2010 ዓ.ም. ወዲህ አዲስ አሸናፊ አትሌት የሚጠበቅበት የወንዶቹ ፉክክር

ከ2006 ዓ.ም. ወዲህ ከተካሄዱት ዘጠኝ የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና የወንዶች ውድድሮች ከአንዱ በስተቀር ሁሉም ድሎች በኤርትራዊው ዘርሰናይ ታደሰ (5) ወይም በጆፍሬይ ካምዎሮር ስም የተመዘገቡ ናቸው፡፡ ዘርሰናይ እና ካምዎሮር በግዲኒያ የማይገኙ በመሆኑም ውድድሩ ከ2010 ዓ.ም. ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ አዲስ የወርቅ ሜዳያ አሸናፊ ስም የሚመዘግብ ይሆናል፡፡ በግዲኒያ የወንዶቹ ፉክክር ማስጀመሪያ ሽጉጥ ሲተኮስ አይኖች ሁሉ ትኩረታቸው ከዚህ በፊት በ21.1 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ተወዳድሮ በማያውቀው የወቅታዊ ምርጥ ብቃት ባለቤት ኡጋንዳዊ አትሌት ጆሹዋ ቼፕቴጊ ላይ ይሆናል፡፡ ኡጋንዳዊው ምንም እንኳን የግማሽ ማራቶን ውድድር ልምድ ባይኖረውም ባለፈው እና በዘንድሮ ዓመት በተለያዩ ውድድሮች ካሳየው ድንቅ ብቃት አንፃር እንደሚጠበቀው ሆኖ እንደሚገኝም ይገመታል፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በኡጋንዳ አትሌቶች ላይ እየታየ የመጣው የብቃት መሻሻል ከዚህ ቀደም ብብርቱ ተፎካካሪነት ከሚታወቁት ኢትዮጵያ እና ኬንያ አትሌቶች በተጨማሪ የዓለም የግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና የወንዶቹን ፉክክር ይበልጥ እንደሚያደምቀው ይጠበቃል፡፡ የኡጋንዳ የወንዶች ቡድን በግማሽ ማራቶን ውድድር የመጀመሪያ ተሳትፎውን በሚያደርገው ጆሹዋ ቼፕቴጊ የሚመራ ሲሆን ሌላኛው ተጠባቂ አትሌት ጃኮብ ኪፕሊሞ፣ አቤል ቼቤት እና ሞሰስ ኪቤትንም አካቷል፡፡

በወንዶቹ ፉክክር ኢትዮጵያውያን አትሌቶችም የቼፕቴጊ ብርቱ ተፎካካሪዎች እንደሚሆኑ ተገምቷል፡፡ በኢትዮጵያ በኩል ሳይጠበቅ ድንቅ ውጤቶችን በማስመዝገቡ ረገድ መልካም ስም ያለው ጉዬ አዶላ ለወርቅ ሜዳያ ድሉ ከተገመቱት መካከል አንዱ ሆኗል፡፡ እ.ኤ.አ. በ2014 በዴንማርክ ኮፐንሀገን ከተካሄደው የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና በፊት ብዙም እውቅና ያልነበረው ቢሆንም የራሱም ምርጥ ሰዓት ከሁለት ደቂቃ በላይ ባሻሻለበት 59፡21 የነሐስ ሜዳልያ አሸናፊ ለመሆን መብቃቱ ይታወሳል፡፡ በዚያው ዓመት መገባደጃ ላይም የወቅቱን የዓለም ግማሽ ማራቶን እና የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮን ጆፍሬይ ካምዎሮር በዴልሂ የግማሽ ማራቶን ፉክርር የራሱን ምርጥ ሰዓት 59.06 በማስመዝገብ ጭምር አሸንፎታል፡፡ ለመጀመሪያ ግዜ በሮጠበት የ2017 የበርሊን ማራቶን ውድድር ላይ ሁለተኛ ሆኖ ሲያጠናቅቅ በመጀመሪያ ተሳትፎ የተመዘገበ የምንግዜም ፈጣን የሆነ 2:03:46 ሰዓት ያለው ጉዬ አዶላ በፖላንዱ የግማሽ ማራቶን ላይ ለመሳተፍ ከተመዘገቡት አትሌቶች መካከል የርቀቱን ሶስተኛ ፈጣን ሰዓት የያዘም ነው፡፡  

በጉዬ አዶላ በሚመራው የኢትዮጵያ ቡድን ውስጥ የግማሽ ማራቶን ፉክክርን ከ60 ደቂቃ በታች ለመጨረስ የበቁና ልምድ ያላቸው አንዳምላክ በልሁ (59:10)፣ ልዑል ገብረስላሴ (59:18) እና አምደወርቅ ዋለልኝ (59:22) እንዲሁም ለዚህ ውድድር መምረጫ በሀገር ውስጥ የተካሄደው የ15 ኪሎ ሜትር ውድድር አሸናፊው ሀይለማሪም ኪሮስ (1:01:08) ተካተዋል፡፡           

የወንዶቹ ፉክክር ያለፉት ሶስት ሻምፒዮናዎች የተናጠል የወርቅ ሜዳልያ ድልን በጆፍሬይ ካምዎሮር አማካይነት አላስቀምስ ያለው የኬንያ የወንዶች ቡድን ዘንድሮም በጠንካራ አትሌቶች የተወከለ ሲሆን በግል የወርቅ ሜልያ ድል ተስፋውን የጣለውም የ2020 የፕራግ ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮን በሆነው ኪቢዎት ካንዲዬ እና የ2017 የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የብር ሜዳልያ አሸናፊው ሊዮናርድ ባርሶቶን ላይ ነው፡፡ ማውሪስ ሙኔኔ፣ በርናርድ ኪፕኮሪር እና በርናርድ ኪሜሊም ሌሎቹ የኬንያ ተወዳዳሪዎች ናቸው፡፡

ሁለቱን የዓለም ሪኮርድ ባለቤቶች የሚያገናኘው የሴቶቹ ፉክክር

እ.ኤ.አ. ከ2011 ጀምሮ ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ አስተዳዳሪ አካል ቤሰቶች የጎዳና ላይ ፉከክሮች ሁለት አይነት የሪኮርድ አመዘጋገብን መከተል ከጀመረ ወዲህ የግድኒያው የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና የሴቶች ውድድር በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ሁለቱን የርቀቱ የዓለም ሪኮርድ ባለቤቶች የሚያፎካክር ይሆናል፡፡ የሴቶቹ ውድድር ከዓለም ሪኮርድ ባለቤቶቹ ኬንያዊቷ ፐሬስ ጄፕቺርቺር (ሴቶች ብቻ የሮጡበት ሪኮርድ ባለቤት) እና ኢትዮጵያዊቷ አባበል የሻነህ (ሴቶች ከወንዶች ጋር የሮጡበት የዓለም ሪኮርድ ባለቤት) በተጨማሪ ያለፈው የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮን ኢትዮጵያዊቷ ነፃነት ጉደታም የአሸናፊነት ክብሯን ለማስጠበቅ የምትፎካከርበት ነው፡፡

በ2016 ካርዲፍ ላይ የተካሄደው የዓለም ግማሽ ማራቶን አሸናፊነት ገድልም ያላት የ27 ዓመቷ ኬንያዊት ፐሬስ ጄፕቺርቺር በ2017 እና 2018 በወሊድ ምክንያት ከውድድር ርቃ ከከረመች በኋላ በ2019 ባደረገቻቸው ውድድሮች ወደ ምርጥ አቋሟ መመለሷን አሳይታለች፡፡ ያም ሆኖ በ2016 በተፎካከሩበት የዴልሂ ግማሽ ማራቶን በጄፕቺርቺር ላይ የበላይነቱን የወሰደችው ኢትዮጵያዊቷ አባበል የሻነህ በግዲኒያም ብርቱ ተፎካካሪዋ እንደምትሆን አያጠራጥርም፡፡ በ2013 የሞስኮ ዓለም ሻምፒዮና እና በ2016ቱ የሪዮ ኦሊምፒክ የ10000 ሜትር እና 5000 ሜትር ተሳትፎዋ ብዙም አመርቂ የሚባል ውጤት ያላስመዘገበችው አባበል ከዛ በኋላ አብዛኛውን ግዜዋን ለጎዳና ላይ ሩጫዎች ሰጥታ ስትሰራ ቆይታለች፡፡ ከተሳተፈችባቸው አስራ ሁለት የግማሽ ማራቶን ውድድሮችም በአስሩ የመጀመሪያዎቹን ሁለት ደረጃዎች በመያዝ ማጠናቀቅ የቻለች ሲሆን ባለፈው ዓመት በተወዳደረችበት የቺካጎ ማራቶን ላይም የራሷ ምርጥ በሆነ 2፡20፡51 ሰዓት ሁለተኛ ሆና ጨርሳለች፡፡

የግድኒያው የሴቶች ግማሽ ማራቶን ዓለም ሻምፒዮና ሌላኛዎቹ የትኩረት ማዕከሎች ሁለቱ የከዚህ ቀደም ሪኮርድ ባለቤት እንዲሁም ከሁለት ዓመት በፊት በስፔን ቫሌንሲያ በተካሄደው የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና የወርቅ እና የብር ሜዳልያ አሸናፊዎች ኢትዮጵያዊቷ ነፃነት ጉደታ እና ኬንያዊቷ ጆሴሊን ጄፕኮስጋይ ናቸው፡፡ ነፃነት ከሁለት ዓመት በፊት በቫሌንሲያ የቅድመ ውድድር ተጠባቂዋ ጄፕኮስጋይን በማስከተል ሻምፒዮን ስትሆን የገባችበት ሰዓት ሴቶች ብቻ የሮጡበት ሪኮርድ ባለቤት አድርጓት ነበር፡፡ ሆኖም ከዛ በኋላ ግን ላለፉት ሁለት ዓመታት አንድም የግማሽ ማራቶን ውድድር ማሸነፍ አልቻለችም፡፡ ጄፕኮስጋይ አሁንም ሙሉ በሙሉ ሪኮርዶችን ወደሰባበረችበት የ2017 ዓ.ም. ድንቅ አቋሟ መመለስ ባትችልም ባለፈው ዓመት በመጀመሪያ የማራቶን ውድድር ተሳትፎዋ የኒው ዮርክ ማራቶንን ለውድድር ስፍራው ሪኮርድ በቀረበ ሰዓት ለማሸነፍ ችላለች፡፡ ሁለቱ አትሌቶች ባለፉት ሁለት ዓመታት አቋማቸው እምብዛም አመርቂ የነበረ ባይሆንም የግድኒያውን ውድድር ዳግም ወደውጤት ከፍታ የሚወጡበት መድረክ ለማድረግ የሚችሉትን ሁሉ እንደሚያደርጉ ይጠበቃል፡፡

በኢትዮጵያ እና ኬንያውያን አትሌቶች መካከል ብርቱ ትንቅንቅ እንደሚደረግበት በሚጠበቀው የሴቶቹ ውድድር በኢትዮጵያ በኩል ከአባበል እና ነፃነት በተጨማሪ ያለምዘርፍ የኋላው፣ ዘይነባ ይመር እና መሰረት ጎላ የሀገራቸውን ሰንደቅ በዓለም አደባባይ ከፍ እንዲል ለማድረግ የሚፎካከሩ አትሌቶች ናቸው፡፡ በኬንያ በኩልም ሮዝመሪ ዋንጂሩ፣ ዶርካስ ኪሜሊ እና ብሪሊያን ኪፕኮኤች በጉጉት የሚጠበቀውን ድል ለማሳካት ከጄፕቺርቺር እና ጄፕኮስጋይ ጎን እንዲሰለፉ የተመረጡት አትሌቶች ናቸው፡፡

የኮሮና ቫይረስ በፍጥነት በዓለም ዙሪያ እየተስፋፋና አሳሳቢነቱ እያደገ በመምጣቱ ምክንያት በርካታ ዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ውድድሮች እንዲሰረዙ ተደርገዋል፡፡ በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ አስተዳዳሪ (ወርልድ አትሌቲክስ) የበላይ ተቆጣጣሪነት እ.አ.አ. በማርች 29/2020 ሊካሄድ ፕሮግራም ተይዞለት የነበረው የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና ለመካሄድ የበቃውም በኮሮና ቫይረስ ወረርሺኝ ምክንያት ለኦክቶበር 17/2020 እንዲተላለፍ ተደርጎ ነው፡፡

በዘንድሮው ውድድር ላይ በ2014 ዓ.ም. ያስመዘገበችውን የወርቅ ሜዳልያ ድል ጨምሮ ባለፉት አስር የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮናዎች የቡድን የሜዳልያ ድል ተቋዳሽ የሆነችው ኤርትራ እንዲሁም ባለፉት 23 የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮናዎች ላይ ያለማቋጥ ተሳታፊ የነበሩት ጃፓን እና አሜሪካ ለመሳተፍ አትሌቶቻቸውን ሳያስመዘግቡ ቀርተዋል፡፡ ካናዳም ውድድሩ ሊካሄድ ጥቂት ቀናት ሲቀሩት ያስመዘገበቻቸውን አትሌቶች በኮሮና ቫይረስ ስጋት ምክንያት ወደ ፖላንድ እንደማትልክ አሳውቃለች፡፡

* የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና አሜሪካ፣ ዩናይትድ ኪንግደም፣ ካናዳ እና ጣሊያንን ጨምሮ ከአስተላላፊዎች ጋር በተናጥል ስምምነት ከተደረሰባቸው 22 ሀገሮች በስተቀር በወርልድ አትሌቲክስ የዩቲዩብ ቻናል ለመላው ዓለም በቀጥታ ይተላለፋል፡፡

Continue Reading

Uncategorized

የኢትዮጵያ ቀን በዋሽንግተን ዲሲ በ’ታላቁ የአፍሪካ ሩጫ’ ዝግጅት ሊከበር ነው – Interview with Dr. Gashaw Abeza

Published

on

By

የኢትዮጵያ ቀን በዋሽንግተን ዲሲ በ’ታላቁ የአፍሪካ ሩጫ’ ዝግጅት ሊከበር ነው – Interview with Dr. Gashaw Abeza
Continue Reading

Uncategorized

#Ethiopia: EthioTube ከስፍራው – Town Hall in DC on Addis Politics – Opening Speech by Ermias Legesse

Published

on

By

#Ethiopia: EthioTube ከስፍራው – Town Hall in DC on Addis Politics – Opening Speech by Ermias Legesse
Continue Reading

Trending