Connect with us

Uncategorized

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የዓለም ዋንጫ ተስፋ ስጋት ውስጥ ገብቷል

Published

on

Waliya vs Congo

Waliya vs Congo

በሩሲያ ለሚካሄደው የ2018ቱ የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የኮንጎ ብራዛቪል አቻውን አስተናግዶ ሽንፈት አጋጥሞታል፡፡ ቀጣዩ ዘገባ የአዲስ አበባ ስታዲየሙን ጨዋታ ለመቃኘት ይሞክራል፡፡

ባለሜዳዎቹ ዋልያዎቹ በቅድመ-ማጣሪያው ሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔን በድምር ውጤት ከረቱ በኋላ ለዚህ ፍልሚያ ሲበቁ ኮንጎዎቹ ድልድሉ ሲደረግ በነበራቸው የተሻለ ወቅታዊ የፊፋ ደረጃ ምክንያት ቅድመ-ማጣሪያ የማድረግ ግዴታ ውስጥ አልገቡም ነበር፡፡ ቡድኖቹ ወደዚህ ጨዋታ የገቡት በደርሶ-መልስ ፍልሚያው ካሸነፉ የመጨረሻውን ምድብ የመቀላቀልን ተስፋ ሰንቀው ነበር፡፡

ለአዲስ አበባው ጨዋታ ቡድኖቹ ወደ ሜዳ ሲገቡ የመጀመሪያ ተሰላፊዎቻቸው የሚከተሉት ነበሩ፡-

ኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን  (4-1-3-2)

ግብ ጠባቂ፡- ታሪክ ጌትነት

ተከላካዮች፡- ስዩም ተስፋዬ ፣ ሰልሀዲን ባርጊቾ፣ አስቻለው ታመነ እና ነጂብ ሳኒ

አማካዮች፡- ጋቶች ፓኖም፣

ሽመልስ በቀለ፣ አስቻለው ግርማ እና በረከት ይስሀቅ

አጥቂዎች፡- ዳዊት ፍቃዱ እና ጌታነህ ከበደ

ተጠባባቂዎች፡- አቤል ማሞ፣ ዋሊድ አታ፣ ዘካሪያስ ቱጂ፣ በኃይሉ ግርማ፣ ኤልያስ ማሞ፣ ቢኒያም በላይ እና ምንይሉ ወንድሙ

ዋና አሰልጣኝ፡- ዮሐንስ ሳህሌ       

 

IMG_2496 copy

ኮንጎ ብራዛቪል ብሔራዊ ቡድን  (4-4-2)

ግብ ጠባቂ፡- ማፎቢ ክርስቶፈር

ተከላካዮች፡- ባውድሪ፣ ንጋንጋ ፍራንሲስ፣ ባቢሌ ሳጊሴ እና ማግኖዜሌ ቢሲኪ

አማካዮች፡- አቮኖ ዱሬል፣ ንዲንጋ ዴልቪን፣ ፋብሪስ ንጉዬሲ እና ንኮንኮ

አጥቂዎች፡- ኩቤምባ ኬቨን እና ቢፎማ ቼቪ

ዋና አሰልጣኝ፡-  ክሎድ ለሯ

በቱኒዚያዊያን አርቢትሮች መሪነት የተጀመረው ጨዋታ ከመነሻው አንስቶ ማራኪ እና አይን የማያስነቅል ነበር፡፡ በተለይ እንግዶቹ ኮንጎ ብራዛቪሎች ኳሱን በመቆጣጠርም ሆነ የጎል እድሎችን በመፍጠር ረገድ ድንቅ ነበሩ፡፡ የክሎድ ለሯ ልጆች የመጀመሪያውን የጎል ሙከራ ያደረጉት በስምንተኛው ደቂቃ ኩቤምባ ኬቨን ለራሱ ክፍተት ፈጥሮ በመሬት ወደ ጎል መትቶ ግብ ጠባቂው ታሪክ ጌትነት ሲይዝበት ነበር፡፡ በ20ኛው ደቂቃ ታሪክ ከራሱ ተከላካዮች ወደ ኋላ የተሰጠውን ኳስ በእጁ በመያዙ ከጎሉ ከሰባት ሜትሮች ርቀት ገደማ በግራ በኩል አዘንብሎ ሁለተኛ ቅጣት ምት ለኮንጎ ተሰጥቷል፡፡ ፋብሪስ ንጉዬሲ ለቢፎማ ቼቪ ያቀበለውን ኳስ የኮንጎው አጥቂ ወደ ጎል ቢመታም የዋልያዎቹ አምበል ስዩም ተስፋዬ በአስደናቂ ጀግንነት ተደርቦ አውጥቶታል፡፡ ኮንጎዎች ያገኙትን የማእዘን ምት ቼቪ አግኝቶ በእግሩ ቢሞክረውም ተደርቦ ወጥቶበታል፡፡ ባለሜዳዎቹ የመጀመሪያ ሙከራቸውን ያደረጉት በ29ኛው ደቂቃ ላይ ነበር፡፡ አስቻለው ግርማ ኳሱን እየገፋ ወደ ፊት ሄዶ ያዘጋጀለትን ሽመልስ በቀለ ወደጎል መትቶ በአግዳሚው ላይ ወጥቶበታል፡፡ በ30ኛው ደቂቃ ጋቶች ፓኖም ከሩቅ የመታው ኳስ ወደውጪ ወጥቶበታል፡፡ በ32ኛው ደቂቃ ሽመልስ ለጌታነህ የሰጠውን የፕሪቶሪያው አጥቂ ወደጎል ሞክሮ በአግዳሚው ላይ ወጥቶበታል፡፡ በ36ኛው ደቂቃ ዳዊት ፍቃዱ ከመሀል የተላከለትን እና እየገፋ ሄዶ የመታው ኳስ ጠንካራ ባለመሆኑ ግብ ጠባቂው በቀላሉ ይዞበታል፡፡ በ41ኛው ደቂቃ ፍፁም ያልተጠበቀ ክስተት ተፈፀመ፡፡ ከሽመልስ በረዥሙ የተላከን ኳስ የመሀል ተከላካዩ ባቤሌ ሳጊሴ ጌታነህ እግር እንዳይደርስ ሲሞክር እንዲሁም ግብ ጠባቂው ማፎምቢ ክርስቶፈር ኳሱን ሊያወጣ ከጎሉ ሲወጣ በመጋጨታቸው ያገኘውን ኳስ ጌታነህ ወደ ጎልነት ቀይሮት ለዋልያዎቹ ያልተጠበቀ መሪነትን አጎናፅፏል፡፡ ይህ መሪነት እና የደጋፊው ደስታ ግን ብዙም አልቆየም፡፡ ከጌታነህ ጎል ሁለት ደቂቃዎች ብቻ በኋላ በኢትዮጵያ የሜዳ ክልል በቀኝ በኩል ከፍፁም ቅጣት ክልል ውጪ ያገኙትን የቅጣት ምት ቼቪ በቀጥታ መትቶ በማስቆጠር እንግዶቹን አቻ አድርጓል፡፡ የግብ ጠባቂው ታሪክ አቋቋም እና ኳሱን ሊያወጣ የሞከረበት መንገድ ብዙ ጥያቄ ቢያስነሳም የቡድኑን አጫጭር ተጨዋቾች ሽመልስ እና አስቻለው ግርማን በግድግዳነት የመጠቀሙ ነገርም ለጎሉ አስተዋፅኦ እንደነበረው ታይቷል፡፡

ከእረፍት መልስ ዋልያዎቹ ተሻሽለው እንደሚመጡ እና በመጀመሪያው አጋማሽ የተወሰደባቸውን የእንቅስቃሴ የበላይነት እንደሚያስመልሱ ቢጠበቅም በተቃራኒው የቀይ ሰይጣኖቹ የበላይነት ልቆ ነበር፡፡ ኮንጎዎቹ በ62ኛው ደቂቃ በአስደናቂ ቅብብል ወደኢትዮጵያ ጎል ደርሰውም ፋብሪስ ንጉዬሲ በቀላሉ ሁለተኛ ጎል አስቆጥሯል፡፡ በ70ኛው ደቂቃ ድንቅ እንቅስቃሴ ሲያደርግ የዋለው ንኮንኮ በግራ በኩል ነጂብ ሳኒን እና ሰልሀዲን ባርጊቾን በቀላሉ አልፎ ሄዶ ለቼቪ በመሬት ያቀበለውን የኤስፓኞል ንብረት የሆነው እና ለግራናዳ በውሰት ተሰጥቶ እየተጫወተ የሚገኘው አጥቂ ወደ ጎል ሞክሮት በታሪክ ተመልሶበታል፡፡ ወዲያውኑም ዋልያዎቹ በጌታነህ የግል ጥረት የሁለተኛው ግማሽ የመጀመሪያ ሙከራቸውን አድርገዋል፡፡ ከሴኮንዶች በኋላም ዳዊት ወደ ጎል ሞክሮ ግብ ጠባቂው ይዞበታል፡፡ በ72ኛው ደቂቃ ሳይታዩ የዋሉት የዋልያዎቹ አለቃ ዮሐንስ ሳህሌ ሁለት ቅያሬዎች አድርገዋል፡፡ የተከላካይ አማካዩ ጋቶች ፓኖም እና የግራ አማካዩ በረከት ይስሀቅ ወጥተው በኃይሉ ግርማ እና ቢኒያም በላይ ተክተዋቸዋል፡፡ በ75ኛው ደቂቃ ከግራ በኩል የተሻገረውን የማእዘን ምት አምበሉ ዴልቪን ንዲንጋ ፍፁም ነፃ ሆኖ በጭንቅላቱ በመግጨት ለቡድኑ ሶስተኛውን ጎል አስቆጥሯል፡፡ በ76ኛው ደቂቃ የሽመልስ ሙከራ በግብ ጠባቂው ተመልሷል፡፡ በ80ኛው ደቂቃ በዋልያዎቹ ተከላካዮች ስህተት የተገኘውን ኳስ ንኮንኮ ተቀይሮ ለገባው ሀርዲ ቢንጉዪላ አቀብሎት የፈረንሳዩ ሊግ 2 ክለብ ኦግዜር አጥቂ አራተኛ ጎል አድርጎታል፡፡ ከሁለት ደቂቃዎች በኋላ ዳዊት ከሽመልስ የተቀበለውን ኳስ አስቆጥሮ የጎል ልዩነቱን ወደሁለት አጥብቧል፡፡ በ88ኛው ደቂቃ ከማእዘን የተሻገረን ኳስ በኃይሉ በጭንቅላቱ ገጭቶ ቢሞክርም በጎሉ አግዳሚ ስር የቆመው ኮንጎ ተከላካይ ጎል ከመሆን ታድጎታል፡፡ ቀይ ሰይጣኖቹ ይህን ኳስ በፈጣን መልሶ ማጥቃት ይዘው ቢሄዱም ሌላኛው ተቀይሮ የገባው ፍራንሲስ ማሎንጋ ክፍት ጎል ላይ ማስቆጠር ተስኖታል፡፡ በባከኑ ደቂቃዎች ላይ ሽመልስ ልዩነቱን የበለጠ ያጠበበ ጎል አስቆጥሮ በኮንጎ ብራዛቪል የ4ለ3 ድል ጨዋታው ተጠናቋል፡፡

ዋልያዎቹ ሲመዘኑ

ግብ ጠባቂ

ታሪክ ጌትነት፡-  የብሔራዊ ቡድኑ ቋሚ ተሰላፊነቱን ያስተማመነ የመሰለው ታሪክ በዋልያዎቹ ማልያ ፈታኙን ቀን አሳልፏል፡፡ ለመጀመሪያው ጎል ቀዳሚ ተጠያቂ ከመሆኑ በተጨማሪ የቡድን መምራት ችግሩ ተጋልጧል፡፡

ተከላካዮች   

ስዩም ተስፋዬ፡- የቡድኑ አምበል በግሉ ከአብዛኞቹ የቡድን አጋሮቹ የተሻለ ቢንቀሳቀስም ቡድኑን በመምራት ረገድ ግን ብዙ ጥያቄ ሊነሳበት ይችላል፡፡

አስቻለው ታመነ፡- ወጣቱ የመሀል ተከላካይ በብሔራዊ ቡድን ህይወቱ መጥፎውን ቀን አሳልፏል ቢባል ግነት አይሆንም፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊሱ ተጨዋች የቢፎማ ቼቪን ፍጥነት እና ጉልበት ለመቋቋም ከመቸገሩ ባሻገር ዴልቪን ንዲንጋ በጭንቅላቱ ላስቆጠረው ጎል ምክንያት ነበር፡፡

ሰልሀዲን ባርጊቾ፡- ሰልሀዲንም እንደ መሀል ተከላካይ አጣማሪው እጅግ ተቸግሮ ውሏል፡፡

ነጂብ ሳኒ፡- የመከላከያው የግራ ተከላካይ በመከላከሉም ሆነ ወደፊት ሄዶ ማጥቃቱን በማገዙ ረገድ ጥሩ አልነበረም፡፡

አማካዮች

ጋቶች ፓኖም፡- ታጋዩ የተከላካይ አማካይ ኳስ በመቀማት፣ በማደራጀትም ሆነ የቡድኑን ሚዛን በመጠበቅ ረገድ እጅግ ደካማ ነበር፡፡

ሽመልስ በቀለ፡- የፔትሮ ጄቱ አማካይ ጎል ቢያስቆጥርም እና ለሌላ ጎል መነሻ ቢሆንም አጠቃላይ እንቅስቃሴው እምብዛም በጥሩነት የሚነገርለት አልነበረም፡፡

አስቻለው ግርማ፡- የሀዋሳ ከነማው መስመር አማካይ/አጥቂ በድፍረት ኳሶችን መቀበሉ ሊያስደንቀው ቢችልም አብዛኞቹ ይበላሹበት ነበር፡፡

በረከት ይስሀቅ፡- ከክለብ አጋሩ አስቻለው ጋር ክንፍ እየተለዋወጠ የተጫወተው በረከት በሜዳ ላይ በቆየባቸው ደቂቃዎች ይህ ነው የሚባል የማጥቃት እንቅስቃሴ ሲያደርግ አልታየም፡፡

አጥቂዎች

ዳዊት ፍቃዱ፡- የደደቢቱ አጥቂ ጎል ቢያስቆጥርም የታወቀ ፍጥነቱን ተጠቅሞ ተጋጣሚዎቹን ማስቸገር፣ ሌላ ፈጠራ ማበርክት አልያም ለአጥቂ አጋሩ እድሎችን መፍጠር ተስኖት ውሏል፡፡

ጌታነህ ከበደ፡- ዳግም ወደ ብሔራዊ ቡድኑ የተመለሰው የፕሪቶሪያ ዩኒቨርሲቲው አጥቂ ከእሱ በሚጠበቅ አጨራረስ ጎል ቢያስቆጥርም እና የመጫወት እና የማሸነፍ ፍላጎቱ ልቆ ቢታይም ወደ ቀድሞ ብቃቱ ለመድረስ ገና እንደሆነ ታይቷል፡፡

ተቀይረው የገቡ

በኃይሉ ግርማ፡- ለመመዘን የሚያበቃ የጨዋታ ጊዜ አልነበረውም፡፡

ቢኒያም በላይ፡- ለመመዘን የሚያበቃ የጨዋታ ጊዜ አልነበረውም፡፡

ዋና አሰልጣኝ፡- ዮሐንስ ሳህሌ       

ቡድኑ በሁሉ ረገድ ደካማ ነበር፡፡ የግል ቴክኒክ እና አካል ብቃት ጉዳዮችን ወደ ጎን ብለን የታክቲክ እና ስነ-ልቦና ጉዳዮችን ብቻ ብናነሳ እጅጉን መበለጣችን በግልፅ የሚታይ ነበር፡፡ የአሰልጣኙ አሰላለፍ፣ ስትራቴጂ፣ ቅያሬዎች፣ ተነሳሽነትን መፍጠር፣ እርማት… ሁሉ ጥያቄዎች ይነሱባቸዋል፡፡

Articles

24ኛው የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና በፖላንድ ግድኒያ ይካሄዳል

Published

on

Gdynia 2020

ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ከምስራቅ አፍሪካ አቻዎቻቸው ጋር ለአሸናፊነት ይፎካከራሉ

በባልቲክ ባሕር ዳርቻ የምትገኘው ትንሿ የፖላንድ ወደብ ከተማ ግድኒያ በሀገራት መካከል የሚካሄድ የዓመቱ ብቸኛ ዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ውድድር የሆነውን እና ከሰዓታት በኋላ የሚጀመረውን የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና ለማስተናገድ ዝግጅቷን አጠናቃለች፡፡ ስመ ጥር አትሌቶች የተካተቱበትና ከ250 በላይ ተሳታፊዎች የሚፎካከሩበት ይህ ሻምፒዮና የዓለም አትሌቲክስ ስፖርት አፍቃሪያን አይኖች ዳግም በምስራቅ አፍሪካውያኑ ኮከቦች ላይ እንዲያተኩሩ እንደሚያስገድድ ይጠበቃል፡፡ በሴቶቹ ውድድር ሴቶች ብቻ የተሳተፉበት ሩጫ የዓለም ሪኮርድ ባለቤቷ ኬንያዊት ፐሬስ ጄፕቺርቺር እና በወንዶች አሯሯጭነት የተመዘገበ የዓለም ሪኮርድ ባለቤት የሆነችው ኢትዮጵያዊቷ አባበል የሻነህ፤ በወንዶች በቅርቡ የ5000 ሜትር እና 10000 ሜትር የዓለም ሪከርዶችን የሰባበረው ኡጋንዳዊው ጆሹዋ ቼፕቴጊ እንዲሁም ኢትዮጵያዊው ጉዬ አዶላ ከሌሎች ተፎካካሪዎቻቸው በመላቅ በፖላንዷ የባህር ዳርቻ ከተማ ላይ የወርቃማ ድል አሻራቸውን ለማሳረፍ ተስፋ ከሚያደርጉት ከዋክብት መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

Photo Aman @angasurunning

ከ2010 ዓ.ም. ወዲህ አዲስ አሸናፊ አትሌት የሚጠበቅበት የወንዶቹ ፉክክር

ከ2006 ዓ.ም. ወዲህ ከተካሄዱት ዘጠኝ የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና የወንዶች ውድድሮች ከአንዱ በስተቀር ሁሉም ድሎች በኤርትራዊው ዘርሰናይ ታደሰ (5) ወይም በጆፍሬይ ካምዎሮር ስም የተመዘገቡ ናቸው፡፡ ዘርሰናይ እና ካምዎሮር በግዲኒያ የማይገኙ በመሆኑም ውድድሩ ከ2010 ዓ.ም. ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ አዲስ የወርቅ ሜዳያ አሸናፊ ስም የሚመዘግብ ይሆናል፡፡ በግዲኒያ የወንዶቹ ፉክክር ማስጀመሪያ ሽጉጥ ሲተኮስ አይኖች ሁሉ ትኩረታቸው ከዚህ በፊት በ21.1 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ተወዳድሮ በማያውቀው የወቅታዊ ምርጥ ብቃት ባለቤት ኡጋንዳዊ አትሌት ጆሹዋ ቼፕቴጊ ላይ ይሆናል፡፡ ኡጋንዳዊው ምንም እንኳን የግማሽ ማራቶን ውድድር ልምድ ባይኖረውም ባለፈው እና በዘንድሮ ዓመት በተለያዩ ውድድሮች ካሳየው ድንቅ ብቃት አንፃር እንደሚጠበቀው ሆኖ እንደሚገኝም ይገመታል፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በኡጋንዳ አትሌቶች ላይ እየታየ የመጣው የብቃት መሻሻል ከዚህ ቀደም ብብርቱ ተፎካካሪነት ከሚታወቁት ኢትዮጵያ እና ኬንያ አትሌቶች በተጨማሪ የዓለም የግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና የወንዶቹን ፉክክር ይበልጥ እንደሚያደምቀው ይጠበቃል፡፡ የኡጋንዳ የወንዶች ቡድን በግማሽ ማራቶን ውድድር የመጀመሪያ ተሳትፎውን በሚያደርገው ጆሹዋ ቼፕቴጊ የሚመራ ሲሆን ሌላኛው ተጠባቂ አትሌት ጃኮብ ኪፕሊሞ፣ አቤል ቼቤት እና ሞሰስ ኪቤትንም አካቷል፡፡

በወንዶቹ ፉክክር ኢትዮጵያውያን አትሌቶችም የቼፕቴጊ ብርቱ ተፎካካሪዎች እንደሚሆኑ ተገምቷል፡፡ በኢትዮጵያ በኩል ሳይጠበቅ ድንቅ ውጤቶችን በማስመዝገቡ ረገድ መልካም ስም ያለው ጉዬ አዶላ ለወርቅ ሜዳያ ድሉ ከተገመቱት መካከል አንዱ ሆኗል፡፡ እ.ኤ.አ. በ2014 በዴንማርክ ኮፐንሀገን ከተካሄደው የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና በፊት ብዙም እውቅና ያልነበረው ቢሆንም የራሱም ምርጥ ሰዓት ከሁለት ደቂቃ በላይ ባሻሻለበት 59፡21 የነሐስ ሜዳልያ አሸናፊ ለመሆን መብቃቱ ይታወሳል፡፡ በዚያው ዓመት መገባደጃ ላይም የወቅቱን የዓለም ግማሽ ማራቶን እና የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮን ጆፍሬይ ካምዎሮር በዴልሂ የግማሽ ማራቶን ፉክርር የራሱን ምርጥ ሰዓት 59.06 በማስመዝገብ ጭምር አሸንፎታል፡፡ ለመጀመሪያ ግዜ በሮጠበት የ2017 የበርሊን ማራቶን ውድድር ላይ ሁለተኛ ሆኖ ሲያጠናቅቅ በመጀመሪያ ተሳትፎ የተመዘገበ የምንግዜም ፈጣን የሆነ 2:03:46 ሰዓት ያለው ጉዬ አዶላ በፖላንዱ የግማሽ ማራቶን ላይ ለመሳተፍ ከተመዘገቡት አትሌቶች መካከል የርቀቱን ሶስተኛ ፈጣን ሰዓት የያዘም ነው፡፡  

በጉዬ አዶላ በሚመራው የኢትዮጵያ ቡድን ውስጥ የግማሽ ማራቶን ፉክክርን ከ60 ደቂቃ በታች ለመጨረስ የበቁና ልምድ ያላቸው አንዳምላክ በልሁ (59:10)፣ ልዑል ገብረስላሴ (59:18) እና አምደወርቅ ዋለልኝ (59:22) እንዲሁም ለዚህ ውድድር መምረጫ በሀገር ውስጥ የተካሄደው የ15 ኪሎ ሜትር ውድድር አሸናፊው ሀይለማሪም ኪሮስ (1:01:08) ተካተዋል፡፡           

የወንዶቹ ፉክክር ያለፉት ሶስት ሻምፒዮናዎች የተናጠል የወርቅ ሜዳልያ ድልን በጆፍሬይ ካምዎሮር አማካይነት አላስቀምስ ያለው የኬንያ የወንዶች ቡድን ዘንድሮም በጠንካራ አትሌቶች የተወከለ ሲሆን በግል የወርቅ ሜልያ ድል ተስፋውን የጣለውም የ2020 የፕራግ ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮን በሆነው ኪቢዎት ካንዲዬ እና የ2017 የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና የብር ሜዳልያ አሸናፊው ሊዮናርድ ባርሶቶን ላይ ነው፡፡ ማውሪስ ሙኔኔ፣ በርናርድ ኪፕኮሪር እና በርናርድ ኪሜሊም ሌሎቹ የኬንያ ተወዳዳሪዎች ናቸው፡፡

ሁለቱን የዓለም ሪኮርድ ባለቤቶች የሚያገናኘው የሴቶቹ ፉክክር

እ.ኤ.አ. ከ2011 ጀምሮ ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ አስተዳዳሪ አካል ቤሰቶች የጎዳና ላይ ፉከክሮች ሁለት አይነት የሪኮርድ አመዘጋገብን መከተል ከጀመረ ወዲህ የግድኒያው የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና የሴቶች ውድድር በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ሁለቱን የርቀቱ የዓለም ሪኮርድ ባለቤቶች የሚያፎካክር ይሆናል፡፡ የሴቶቹ ውድድር ከዓለም ሪኮርድ ባለቤቶቹ ኬንያዊቷ ፐሬስ ጄፕቺርቺር (ሴቶች ብቻ የሮጡበት ሪኮርድ ባለቤት) እና ኢትዮጵያዊቷ አባበል የሻነህ (ሴቶች ከወንዶች ጋር የሮጡበት የዓለም ሪኮርድ ባለቤት) በተጨማሪ ያለፈው የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮን ኢትዮጵያዊቷ ነፃነት ጉደታም የአሸናፊነት ክብሯን ለማስጠበቅ የምትፎካከርበት ነው፡፡

በ2016 ካርዲፍ ላይ የተካሄደው የዓለም ግማሽ ማራቶን አሸናፊነት ገድልም ያላት የ27 ዓመቷ ኬንያዊት ፐሬስ ጄፕቺርቺር በ2017 እና 2018 በወሊድ ምክንያት ከውድድር ርቃ ከከረመች በኋላ በ2019 ባደረገቻቸው ውድድሮች ወደ ምርጥ አቋሟ መመለሷን አሳይታለች፡፡ ያም ሆኖ በ2016 በተፎካከሩበት የዴልሂ ግማሽ ማራቶን በጄፕቺርቺር ላይ የበላይነቱን የወሰደችው ኢትዮጵያዊቷ አባበል የሻነህ በግዲኒያም ብርቱ ተፎካካሪዋ እንደምትሆን አያጠራጥርም፡፡ በ2013 የሞስኮ ዓለም ሻምፒዮና እና በ2016ቱ የሪዮ ኦሊምፒክ የ10000 ሜትር እና 5000 ሜትር ተሳትፎዋ ብዙም አመርቂ የሚባል ውጤት ያላስመዘገበችው አባበል ከዛ በኋላ አብዛኛውን ግዜዋን ለጎዳና ላይ ሩጫዎች ሰጥታ ስትሰራ ቆይታለች፡፡ ከተሳተፈችባቸው አስራ ሁለት የግማሽ ማራቶን ውድድሮችም በአስሩ የመጀመሪያዎቹን ሁለት ደረጃዎች በመያዝ ማጠናቀቅ የቻለች ሲሆን ባለፈው ዓመት በተወዳደረችበት የቺካጎ ማራቶን ላይም የራሷ ምርጥ በሆነ 2፡20፡51 ሰዓት ሁለተኛ ሆና ጨርሳለች፡፡

የግድኒያው የሴቶች ግማሽ ማራቶን ዓለም ሻምፒዮና ሌላኛዎቹ የትኩረት ማዕከሎች ሁለቱ የከዚህ ቀደም ሪኮርድ ባለቤት እንዲሁም ከሁለት ዓመት በፊት በስፔን ቫሌንሲያ በተካሄደው የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና የወርቅ እና የብር ሜዳልያ አሸናፊዎች ኢትዮጵያዊቷ ነፃነት ጉደታ እና ኬንያዊቷ ጆሴሊን ጄፕኮስጋይ ናቸው፡፡ ነፃነት ከሁለት ዓመት በፊት በቫሌንሲያ የቅድመ ውድድር ተጠባቂዋ ጄፕኮስጋይን በማስከተል ሻምፒዮን ስትሆን የገባችበት ሰዓት ሴቶች ብቻ የሮጡበት ሪኮርድ ባለቤት አድርጓት ነበር፡፡ ሆኖም ከዛ በኋላ ግን ላለፉት ሁለት ዓመታት አንድም የግማሽ ማራቶን ውድድር ማሸነፍ አልቻለችም፡፡ ጄፕኮስጋይ አሁንም ሙሉ በሙሉ ሪኮርዶችን ወደሰባበረችበት የ2017 ዓ.ም. ድንቅ አቋሟ መመለስ ባትችልም ባለፈው ዓመት በመጀመሪያ የማራቶን ውድድር ተሳትፎዋ የኒው ዮርክ ማራቶንን ለውድድር ስፍራው ሪኮርድ በቀረበ ሰዓት ለማሸነፍ ችላለች፡፡ ሁለቱ አትሌቶች ባለፉት ሁለት ዓመታት አቋማቸው እምብዛም አመርቂ የነበረ ባይሆንም የግድኒያውን ውድድር ዳግም ወደውጤት ከፍታ የሚወጡበት መድረክ ለማድረግ የሚችሉትን ሁሉ እንደሚያደርጉ ይጠበቃል፡፡

በኢትዮጵያ እና ኬንያውያን አትሌቶች መካከል ብርቱ ትንቅንቅ እንደሚደረግበት በሚጠበቀው የሴቶቹ ውድድር በኢትዮጵያ በኩል ከአባበል እና ነፃነት በተጨማሪ ያለምዘርፍ የኋላው፣ ዘይነባ ይመር እና መሰረት ጎላ የሀገራቸውን ሰንደቅ በዓለም አደባባይ ከፍ እንዲል ለማድረግ የሚፎካከሩ አትሌቶች ናቸው፡፡ በኬንያ በኩልም ሮዝመሪ ዋንጂሩ፣ ዶርካስ ኪሜሊ እና ብሪሊያን ኪፕኮኤች በጉጉት የሚጠበቀውን ድል ለማሳካት ከጄፕቺርቺር እና ጄፕኮስጋይ ጎን እንዲሰለፉ የተመረጡት አትሌቶች ናቸው፡፡

የኮሮና ቫይረስ በፍጥነት በዓለም ዙሪያ እየተስፋፋና አሳሳቢነቱ እያደገ በመምጣቱ ምክንያት በርካታ ዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ውድድሮች እንዲሰረዙ ተደርገዋል፡፡ በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ አስተዳዳሪ (ወርልድ አትሌቲክስ) የበላይ ተቆጣጣሪነት እ.አ.አ. በማርች 29/2020 ሊካሄድ ፕሮግራም ተይዞለት የነበረው የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና ለመካሄድ የበቃውም በኮሮና ቫይረስ ወረርሺኝ ምክንያት ለኦክቶበር 17/2020 እንዲተላለፍ ተደርጎ ነው፡፡

በዘንድሮው ውድድር ላይ በ2014 ዓ.ም. ያስመዘገበችውን የወርቅ ሜዳልያ ድል ጨምሮ ባለፉት አስር የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮናዎች የቡድን የሜዳልያ ድል ተቋዳሽ የሆነችው ኤርትራ እንዲሁም ባለፉት 23 የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮናዎች ላይ ያለማቋጥ ተሳታፊ የነበሩት ጃፓን እና አሜሪካ ለመሳተፍ አትሌቶቻቸውን ሳያስመዘግቡ ቀርተዋል፡፡ ካናዳም ውድድሩ ሊካሄድ ጥቂት ቀናት ሲቀሩት ያስመዘገበቻቸውን አትሌቶች በኮሮና ቫይረስ ስጋት ምክንያት ወደ ፖላንድ እንደማትልክ አሳውቃለች፡፡

* የዓለም ግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና አሜሪካ፣ ዩናይትድ ኪንግደም፣ ካናዳ እና ጣሊያንን ጨምሮ ከአስተላላፊዎች ጋር በተናጥል ስምምነት ከተደረሰባቸው 22 ሀገሮች በስተቀር በወርልድ አትሌቲክስ የዩቲዩብ ቻናል ለመላው ዓለም በቀጥታ ይተላለፋል፡፡

Continue Reading

Uncategorized

የኢትዮጵያ ቀን በዋሽንግተን ዲሲ በ’ታላቁ የአፍሪካ ሩጫ’ ዝግጅት ሊከበር ነው – Interview with Dr. Gashaw Abeza

Published

on

By

የኢትዮጵያ ቀን በዋሽንግተን ዲሲ በ’ታላቁ የአፍሪካ ሩጫ’ ዝግጅት ሊከበር ነው – Interview with Dr. Gashaw Abeza
Continue Reading

Uncategorized

#Ethiopia: EthioTube ከስፍራው – Town Hall in DC on Addis Politics – Opening Speech by Ermias Legesse

Published

on

By

#Ethiopia: EthioTube ከስፍራው – Town Hall in DC on Addis Politics – Opening Speech by Ermias Legesse
Continue Reading

Trending